ሳይፀልዩ_ማደር

/በረከት በላይነህ/
የተራበ ነብር ከሩቅ ተመልክታ
ሚዳቋ ፀለየች….
“አውጣኝ አውጣኝ” አለች ለፈጠራት ጌታ

ነብሩም ተርቦ
ወደ አምላኩ ቀርቦ
ሚዳቆዋን አይቶ – አንጀቱ ከሆዱ እንደተጣበቀ
ፈቅዶ እንዲሰጠው – አምላኩን ጠየቀ

የሁላችን ሰሪ
ፀሎታቸውንም ሰማቸው ፈጣሪ
አምላክም በድምፁ ሚዳቆዋን አላት
“ሩጠሽ አምልጪ ከበረታው ጠላት”

ነብሩንም አለው – “እሩጥ ተከተላት ምግብ አርገህ ብላት”
ሚዳቆዋ ስትሮጥ
ከነብር ለማምለጥ
ነብሩም ሲከተላት
ሆዱን ሊሞላባት

ቋጥኙን ስትዘል እግሯ ተስፈንጥሮ
ሆዱን ብትረግጠው የተኛው ከርከሮ
ከእንቅልፉ ሲነቃ ልክ ሲደነብር
ጉሮሮውን ያዘው የፀለየው ነብር

አውጣኝ ያለው ወጥቶ አብላኝ ያለው በላ
ሳይፀልይ ያደረው ከርከሮ ተበላ።

Published by 𝗬𝗮𝘀𝗶𝗻 𝗘𝗻𝗱𝗿𝗶𝘀

Bloger

Leave a comment

Design a site like this with WordPress.com
Get started